Saturday, April 22, 2017

ተናጋሪ ፖስተሮች

ማስታወቂያ ሰፊ ጽንሰ ሐሳብ ነው፡፡ በርካታ ዘርፎችም አሉት፡፡ የራሱ የክዋኔ ስርዓት እና ብልሃትም እንዲሁ…ከዚህ ሰፊ ባህር አንዲት ቀጭን ሰበዝ መዘን ለዛሬ ጨዋታችን የሃሳብ ምህዋር መሽከርከሪያነት ልንፈቅድ ነው፡፡
 
በአንድ ወገን አድጓል በሌላው አላደገም፤ በአንዱ ጎጥ ኢንዱስትሪ ነው በሌላው አይደለም፤ በአንዱ ጎራ ባህል አጥፍቷል በሌላው ይገነባል . . .  እያስባለ በማከራከር ላይ ስላለው የኢትዮጵያ ፊልም ከፊልምም ስለ ፖስተሮች /የስዕል ማስታወቂያዎች/ እናውጋ
ማሳወቅ፣ ለተጠቃሚነት መገፋፋት (ማጓጓት)፣ ዘላቂ ደንበኛ ማድረግ -ዋና ዋናዎቹ የማስታወቂያ ዓላማዎች ናቸው፡፡ በርግጥ በማስታወቂያ ዙሪያ ስምምነት ላይ ያልተደረሰባቸው ጉዳዮች አሁንም አሉ፡፡ ማስታወቂያ ሳይንስ ነው ወይስ ጥበብ፤ ዓላማው ማታለል፣ ማሳመን፣ ወይስ ማስገደድ . . .ሌሎችም ቁርጥ ያለ ምላሽ ያልተሰጣቸው ሃሳቦችን ከነክርክራቸው አሁንም እንደተሸከመ ነው፡፡

Friday, January 13, 2017

መልክን የሻሩ ዘፈኖች

እያንዳንዳቸው የጥበብ ስራዎች የተሰሩበትን ዘመን አስተሳሰብ፣ ምኞት እና አኗኗር የሚያሳዩ መስታወቶች ናቸው፡፡

‹‹ፈረንጅ ሃገር ሳትሄድ ገና እዚሁ ሳለህ

የገባኸውን ቃል እንዴት ታፈርሳለህ?

የእውነት ሰው መስለኸኝ ክቡር የከበረ

ቃልኪዳኔን ይዤ ጠብቄህ ነበረ ››

የሚለው በብዙነሽ በቀለ የተዜመ ግሩም ዘፈን ብዙ ወጣቶች ለትምህርት ወደ ውጪ ሃገራት የሚሄዱበት፤ ትምህርታቸውን አጠናቀው በሚመለሱበት ጊዜ ደግሞ በአስተሳሰብ ልዩነት ወይም በሌላ የራሳቸው ምክንያት ከቀድሞ ወዳጆቻቸው የሚለያዩበት እንደነበረ መገመት ይቻላል፡፡

Monday, December 7, 2015

ያለመግባባታችን ምንጭ በጣም መግባባታችን ነው!

አየሽ እኔ እና አንቺ በጣም ተግባብተናል፡፡ ተገባብተናል፡፡ እኔ አንቺ ውስጥ. . . አንቺም እኔ ውስጥ. . . አሳምረሽ ገብተሸኛል፡፡ በትክክል ገብቼሻለሁ፡፡ ዘላቂ መግባባታችን የወለደው አለመግባባት እዚህ ጋር ይፀነሳል፡፡

ሀሳቤን ብቻ ሳይሆን የሀሳብ መንገዴን አግኝሽዋል፡፡ የውሸቴን መነሾ እስከ መድረሻና ውጤቱ መናገር ሳልጀምር አውቀሽዋል፡፡ ፊቴ ላይ የሚሯሯጠው ደም ካዘለው ስሜት በላቀ በልቦናዬ
ያፈንኩትን ሀቅ መገንዘብ ችለሻል፡፡

Wednesday, August 12, 2015

የማስታወቂያዎቻችን ነገር

‹ሱዛን ፎርማን› የተባሉ ጸሐፊ ‹‹The Media of Advertising›› በተሰኘው መጽሐፋቸው ስለ ማስታወቂያ አጀማመር ሲገልጹ 

‹‹ማስታወቂያ ስረ መሰረቱ በጥንታዊት ሮም መኳንንቶችን ለማስደሰት የሚደረጉ ድብድቦች /Gladiators/ በታላላቅ አደባባዮች የሚካሄዱ መሆኑን የሚያስተዋውቁ፤ በመካከለኛው ዘመን የሞት ፍርድ በአደባባይ የሚፈፀም መሆኑን የሚያመላክቱ፤ በአሜሪካ ጠረፍ በትልቁ ተፅፈው የሚንጠለጠሉ የ ’ወንጀለኛ ይፈለጋል’ ማሳሰቢያዎች ናቸው፡፡›› ይላሉ፡፡

በግብጽ በ 3200 ዓ.ዓ አካባቢ በተሰሩ የማምለኪያ ህንፃዎች ላይ ማንኛው ንጉስ እንዳስገነባው የሚጠቁሙት ጽሁፎች ከማስታወቂያ ይመደባሉ የሚሉ ምሁራንም አሉ፡፡

በታሪክ የመጀመሪያው ተብሎ በ (Encyclopedia Britanica,Vol 1 ,180) የተመዘገበው የጽሁፍ ማስታወቂያ 

‹‹ሼም የተባለው ባሪያ ሃፑ ከተሰኘው አሳዳሪ ተሰውሯል፡፡ ሃፑ የቴቢስ መልካም ዜጎች ሁሉ ይህን የጠፋ ባሪያ ቢመልሱለት ይወዳል፡፡ ባሪያው ባለቡናማ ዓይን ነው፡፡ ያለበትን አካባቢ ዜና ላመጣ ግማሽ የወርቅ ሳንቲም ይሰጠዋል፡፡ ሼምን ወደአሳዳሪው ለሚመልስ ደግሞ እንደፍላጎቱ ልብስ የሚደሸመንለት ሲሆን ሙሉ የወርቅ ሳንቲምም ይሰጠዋል፡፡››

የሚል ሲሆን ከ 3ሺህ ዓመት በፊት በፓፒረስ ላይ የተጻፈ መሆኑ ተገልጧዋል፡፡
በዘመናዊና በተደራጀ መልኩ ከቀረቡት ማስታወቂያዎች በፊት ግን ሰዎች ድምጻቸውን ከፍ በማድረግ ማስታወቂያቸውን ይናገራሉ፡፡ በሐገራችንም ይህ ተግባር የተለመደ ነበር

Tuesday, July 14, 2015

‹ስለ ኢትዮጵያ ስል ተኮላሽቻለሁ፡፡›

‹‹ፍቅር ይዞህ ያውቃል ለመሆኑ?››
‹‹አዎን››
‹‹ከማን ጋር?››
‹‹ከኢትዮጵያ››
‹‹አሃ! የፍቅረኛህ ስም ኢትዮጵያ ነበር?››
‹‹አዎን!››
‹‹ለምን ከኢትዮጵያ ጋር ተለያያችሁ?››
‹‹መንግስቱ ሃይለማርያም እና ድርጅቱ ትግላችንን እና ኢትዮጵያ ሀገራችንን ገደሏት››
‹‹ዋለልኝ! ለምን ታሾፍብኛለህ? ምንድነው የምትቀባጥረው?››


ከጭምትነቱ ወጥቶ ጣራው እስኪሰነጠቅ ድረስ ሳቀ፡፡ ቲያትር የሚሰራ ነው የሚመስለው፡፡ ለደቂቃዎች ሳቁን አላቆመም፡፡ ሳቁ ግን የደስታ ሳይሆን የንዴት እንደነበር ያስታውቃል፡፡ አይኖቹ እና ፊቱ ቀሉ፡፡ ደምስሮቹ በአንገቱ እና በፊት ገጹ ላይ ተገታተሩ፡፡ የመጨረሻ ጥያቄዬ በጣም እንዳበሳጨው ተረዳሁ፤

Monday, November 17, 2014

ከብዙ ዓመታት በኋላ የሚነገር የከብዙ ዓመት በፊት ታሪክ



መግቢያ


ጥቂት የማይባሉ አያሌ ዘመናትን ወደፊት ተሻግረን ከቀናቶች መካከል ባለ የተለመደች አዘቦት ቀን ላይ ነን፡፡ ተንጠራርተን እያስተዋልናት ባለችው በዚህች ተራ ቀን  ድሮ ምን ይመስል እንደነበር ልንቃኝ ነው፡፡ በአሁን የጊዜ ፈረስ ተፈናጠን ነገን በዛሬ ልናነፃፅር . . .


ትዝታ አይደለም፡፡ ትዝታ የኖሩትን በምናብ መድገም ነው፡፡ ከትውስታ ጓዳም ከህልውና መድረክም ሊሰርዙት አይቻልም፡፡ መከሰቱም ማለፉም የተረጋገጠ ነው፡፡

 
ትንቢት አይደለም፡፡ ትንቢት ያልኖሩትን መገመት ነው፡፡ ስምረቱንም ክሽፈቱንም ማረጋገ ከባድ ነው፡፡
ይህ ከሁለቱም ይለያል፡፡ ሁለቱንም መሳይ ገፅ አለው፡፡

Tuesday, September 9, 2014

ጉዞ


(ንዑስርዕስ ) ወደብርሀን
የምንገኘው ብርሀን ከሚታደልበት ብርሀን ውስጥ ነው። የብርሀን ማነስ ድንግዝግዝን ካወፈረበት ዓለም። ብርሐን ማለት ዕውቀት ነው። ዕውቀት ማለት እውነት፣  እውነት ማለት ውበት ማለት ነው። ሐቀኛ ውበት ከልከኛ እና ከቀና እውነት ይወለዳል። ውበት ሁሉ እውነት አይደለም። እውነት ሁሉ ውበት አይደለም። በሀቅ ካባ የተጀቦነ - በበግ ለምድ የተሸሸገ ተኩላዊ እውነት አለ። በሽንገላ ከንፈር ማንነቱን የተነጠቀ እውነት አለ። ብልጭልጭ የጋረደው። አርቴፊሻል ውበት አለ በብልጭልጭ ብዛት፣ በወከባ ብዛት፣ በግርግር ብዛት ውበት ማማ ላይ የተሰቀለ። የድንጋሪው ማጥሪያ ወንፊት ማስተዋል ነው። ማስተዋል። በመገለጡ ውስጥ ያለውን ቅኔ መፍታት።

ግስጋሴው ወደፊት ነው። ፈትለፊቱ ድንበር የለውም። ጫፉ መሻት ነው። ዕውቀትን መሻት። ጥልቀትን፣ ምጥቀትን፣ ስፋትን፣ ርዝመትን መሻት . . . ሁሉም በፍላጎት ነጻ ፈቃድ የሚወለዱ፤ በጥረት እልህ አስጨራሽ ትጋት የሚያድጉ እና የሚጎለምሱ ነገዎች ናቸው። የዕውቀት ኬላ ማማዎች . . . ያልደረሱበትን፣ ያመረመሩትን እየጓጉ የሚናፍቁበት፤ የያዙትን አጣጥመው የተሻለ የሚማትሩበት፤ እንደመሰላል ያለ የከፍታ አጋዥ። ተንጠራርተው እየጨበጡ። የጨበጡትን ሳይረግጡ ይልቁንም ባለው ላይ እየደመሩ። የመንገዱ መቋጫ እርካታ ነው። ደረስኩ፣ በቃሁ፣ ነቃሁ፣ በሰልኩ፣ ባሉበት ቅጽበት የጉዞው ምዕራፍ ይዘጋል። ‘ብርሀናማ ጨለማ’ን ‘ወርቃማብርሀን’ ነው ብሎ በማምለክ ቅያስ ውስጥ መዳከር ይጀመራል። . . .

Friday, August 22, 2014

0(ዜሮ)


‹‹ከቁጥሮች መካከል የመጨረሻውን ባዶ ደረጃ የያዘችው ‘0’ ናት፡፡ አንተም በሰው ልጆች የዕውቀት፣ የዐስተሳሰብና የዐመለካከት መስፈርቆች ስትገመገም ማርክህ ዜሮ ቢሆን ’ዋጋ የለኝም’ አትበል፡፡
ያቺ . . . የቁጥሮች ሁሉ አናሳ ዜሮ በሙሉ ቁጥሮች ስሌት ወቅት ቀዳሚውን የፊት ወንበር ትቆናጠጥ እንጂ፣ ዋጋ ባላቸው የመቁጠሪያ ቁጥር መገልገያዎች እርሷን ከፊትለፊት ቦታ ያስቀደመ ትርጉም አልባ ድምሮችን ከማንኳተቱ በተጓዳኝ አላዋቂነቱን ያሳብቃል፡፡ ታዲያ . . . አንተና መሰሎችህ አጠቃላይ ሰዋዊ ውጤታችሁ ዜሮ ሆኖ ሳለ ከሁሉም ፊት መቆማችሁ፣ ሙሴነትን መተግበራችሁ ይቅርና ለማሰብ መነሳሳታችሁ ራሱ ከስህተት በላይ ነው፡፡ 
ዜሮ ከፍ ካሉ ቁጥሮች መካከል አለያም ከበስተኋላ በተከታይነት ስትቆም የምታሳየውን ትርጉም አዘል ለውጥ አስተውል፡፡ ራስ በመሆን ብቻ ሳይሆን ጭራ በመሆንም ግዙፍ ለውጥ አምጪ ታሪክ መስራት ይቻላል፡፡ ራስህን ሁን፡፡ ››

Thursday, August 14, 2014

አጣብቂኝ



ላለው ይጨመርለታል። ብር ላለው ወርቅ፤ ጠገራ ላለው ማርትሬዛ፤ መከራ ላለው ፍዳ ይጨመርለታል። ትላንት የተጨመሩለትን አሰበ። በዲግሪ ላይ ስራ፤ በስራ ላይ ረብጣ፤ በገንዘብ ላይ ቆንጆ ሚስት፤ በሚስት ላይ ውብ ልጅ ተጨምረውለታል። ደስታቸውን እያጣጣመ አልፏቸዋል። በሚገባ ተጠቅሞባቸዋል። ኖሯቸዋል።

ሁለተኛውን ምዕራፍ ግን በአግባቡ ማስተናገድ አቃተው። ሳቅን የሚያውቅ የልቅሶን ጣዕም ለመረዳት ከሳቁ መንፈስ በሀሳብም በምግባርም መውጣት እንዳለበት ዘነጋ። እሱ መከራ፣ ፈተና . . . ብሎ የገለጸውን የህይወት ክፍል በብቃት መተወን ተሳነው። ቀድሞ በበጎ ገጹ ሳለ“ተጨመረልኝ” ሲል በ ‘ለኔ’ የገለጸውን አሁን“ ተጨመረብኝ” በማለት በ ‘እኔ ላይ’ አደረገው።

በትላንትናው ውስጥ የገነባው የኑሮ ግንብ የእንቧይ ካብ የሚሆንባቸውን ምክንያቶች በቅደም ተከተል ደረደረ።
*ውብ ፍሬው ካለማወቅ ብርሀን ታመልጥ ዘንድ፤ ክፉውን እና በጎውን በሚያስለየው የዕውቀት ጠበል ትጠመቅ ዘንድ እንዳትችል ኪሱ ከስቷል።

Monday, August 4, 2014

አየህ ወዳጄ . . .



እንደ ዕድል ሆኖ ዛሬ ከማይክራፎኑ ጅርባ ነህ፡፡ እንዳጋጣሚ ሆኖ ብዕርህ የብዙዎችን አትኩሮት ስቧል፡፡ወደውም ሳይወዱም ይሰሙሀል፡፡ ምርጫ ያጣም አማራጭ የፈለገም ያነብሀል፡፡

 እዚህ ጋር ቆም ብለህ አስብ . . .

ይህ ውድ መዓድ፣ በርካቶች ፈልገው ያጡት፤ በርካቶች ከኔ የተሻለ ይጠቀምበት ብለውበትህትና ያለፉት መድረክ የተከበረ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ነገር ተበላሽቶ ማንም ፈነጨበት እንጂ . . .