በአንድ ቲያትርን በሚያስተምር መንግስታዊ ተቋም የሚሰለጥን ሰው ነው። ፒሪሪም ፓራራም ለተባለ ፊልም በተዋናይነት ይታጫል። ታጭቶም አልቀረም ስክሪን ቴስት አድርጎ ያልፋል። ይተውናልም . . .
የተሰጠችው ቦታ አጠር ያለች ብትመስልም ረዘም ላሉ ደቂቃዎች ከ አንድ ለበለጡ ቀናት ይቀረጻል። ፊልሙ የዝግጅት ጣጣውን ጨርሶ ለእይታ ሲበቃ ሰዎችን እንዲጋብዝ የተሰጠው ወረቀት ፊልሙ ላይ ካለው ቦታ የበለጠ ነበር። የቀረው ዘመድ አዝማድ የለም። አብረውት የሚማሩ በሙሉ ታዳሚዎች ናቸው።
ለአብዛኞቹ እሱ ለጋበዛቸው እድምተኞች አንድ ቀን ከምናምን ሙሉ ያሳለፈውን አድካሚ የቀረፃ ጊዜ ተርኳል። ስክሪፕቱን ለመያዝ የፈጀበትን ጊዜ አውርቷል። የዳይሬክተሩን ቁጡነት ለፍፏል። ስለተዋንያን፣ ስለካሜራ ደስኩሯል።
አሁን ፊልሙ በመታየት ላይ ነው። አጋማሹ ላይ የደረሰ ቢሆንም ተዋናዩ እስካሁን አልታየም። ከግማሽ አልፎ ወደመጠናቀቁ ሲቃረብ ተዋናዩ ውልብ ብሎ ጭልም ቢልም፣ ጥቂት ቃላትን ተናግሮ ድምጹን ቢያሰማም ያላስተዋሉት በዙ።
‘’ታይቷል!’’ ‘’አልታየም!’’ እያሉ የሚከራከሩ በረከቱ።
በበነጋው የተቀረጸው ብዙ እንደነበር ነገር ግን ሰዓት ለማሳጠር እና በአናዳንድ የኤዲቲንግ ስህተቶች ምክንያት በዚህ መልኩ እንዳጠረ . . . ይህ በመሆኑም ፕሮሪውሰሩን እና ዳይሬክተሩን ጨምሮ በርካታ የፊልሙ አባላት እንዳዘኑ ለወዳጆቹ ለማስረዳት እያሰበ ወደሚማርበት ቦታ ሲደርስ- ምክንያቱን ከመግለፁ በፊት፣ ችግሩን ከማስረዳቱ በፊት፣ ምንም ከማለቱ ምንም ነገር ከማድረጉ በፊት ጥቁር ሰሌዳው ላይ የተፃፈውን ሲያነብ ቅስሙ የተሰበረው - የተበሳጨውና የተናደደው - ነገርየው የተባለው እሱ ለይ በመሆኑ እንጂ ባይሆን ኖሮ ከተከት ብሎ በሳቀ ነበር። ጥቁሩ ግድግዳ ላይ በነጭ የተነቀሰው ጽሁፍ እንዲህ የሚል ነው።
የአፋልጉኝ ማስታወቂያ
ወዳጃችን እከሌ እከሌ ፒሪሪም ፓራራም የተባለ ፊልም ላይ ገብቶ የገባበት ስለጠፋብን ያለበትን የሚያውቅ ካለ ቢጠቁመን ወሮታውን የምንከፍል መሆኑን እንገልጻለን።