Monday, November 17, 2014

ከብዙ ዓመታት በኋላ የሚነገር የከብዙ ዓመት በፊት ታሪክ



መግቢያ


ጥቂት የማይባሉ አያሌ ዘመናትን ወደፊት ተሻግረን ከቀናቶች መካከል ባለ የተለመደች አዘቦት ቀን ላይ ነን፡፡ ተንጠራርተን እያስተዋልናት ባለችው በዚህች ተራ ቀን  ድሮ ምን ይመስል እንደነበር ልንቃኝ ነው፡፡ በአሁን የጊዜ ፈረስ ተፈናጠን ነገን በዛሬ ልናነፃፅር . . .


ትዝታ አይደለም፡፡ ትዝታ የኖሩትን በምናብ መድገም ነው፡፡ ከትውስታ ጓዳም ከህልውና መድረክም ሊሰርዙት አይቻልም፡፡ መከሰቱም ማለፉም የተረጋገጠ ነው፡፡

 
ትንቢት አይደለም፡፡ ትንቢት ያልኖሩትን መገመት ነው፡፡ ስምረቱንም ክሽፈቱንም ማረጋገ ከባድ ነው፡፡
ይህ ከሁለቱም ይለያል፡፡ ሁለቱንም መሳይ ገፅ አለው፡፡

Tuesday, September 9, 2014

ጉዞ


(ንዑስርዕስ ) ወደብርሀን
የምንገኘው ብርሀን ከሚታደልበት ብርሀን ውስጥ ነው። የብርሀን ማነስ ድንግዝግዝን ካወፈረበት ዓለም። ብርሐን ማለት ዕውቀት ነው። ዕውቀት ማለት እውነት፣  እውነት ማለት ውበት ማለት ነው። ሐቀኛ ውበት ከልከኛ እና ከቀና እውነት ይወለዳል። ውበት ሁሉ እውነት አይደለም። እውነት ሁሉ ውበት አይደለም። በሀቅ ካባ የተጀቦነ - በበግ ለምድ የተሸሸገ ተኩላዊ እውነት አለ። በሽንገላ ከንፈር ማንነቱን የተነጠቀ እውነት አለ። ብልጭልጭ የጋረደው። አርቴፊሻል ውበት አለ በብልጭልጭ ብዛት፣ በወከባ ብዛት፣ በግርግር ብዛት ውበት ማማ ላይ የተሰቀለ። የድንጋሪው ማጥሪያ ወንፊት ማስተዋል ነው። ማስተዋል። በመገለጡ ውስጥ ያለውን ቅኔ መፍታት።

ግስጋሴው ወደፊት ነው። ፈትለፊቱ ድንበር የለውም። ጫፉ መሻት ነው። ዕውቀትን መሻት። ጥልቀትን፣ ምጥቀትን፣ ስፋትን፣ ርዝመትን መሻት . . . ሁሉም በፍላጎት ነጻ ፈቃድ የሚወለዱ፤ በጥረት እልህ አስጨራሽ ትጋት የሚያድጉ እና የሚጎለምሱ ነገዎች ናቸው። የዕውቀት ኬላ ማማዎች . . . ያልደረሱበትን፣ ያመረመሩትን እየጓጉ የሚናፍቁበት፤ የያዙትን አጣጥመው የተሻለ የሚማትሩበት፤ እንደመሰላል ያለ የከፍታ አጋዥ። ተንጠራርተው እየጨበጡ። የጨበጡትን ሳይረግጡ ይልቁንም ባለው ላይ እየደመሩ። የመንገዱ መቋጫ እርካታ ነው። ደረስኩ፣ በቃሁ፣ ነቃሁ፣ በሰልኩ፣ ባሉበት ቅጽበት የጉዞው ምዕራፍ ይዘጋል። ‘ብርሀናማ ጨለማ’ን ‘ወርቃማብርሀን’ ነው ብሎ በማምለክ ቅያስ ውስጥ መዳከር ይጀመራል። . . .

Friday, August 22, 2014

0(ዜሮ)


‹‹ከቁጥሮች መካከል የመጨረሻውን ባዶ ደረጃ የያዘችው ‘0’ ናት፡፡ አንተም በሰው ልጆች የዕውቀት፣ የዐስተሳሰብና የዐመለካከት መስፈርቆች ስትገመገም ማርክህ ዜሮ ቢሆን ’ዋጋ የለኝም’ አትበል፡፡
ያቺ . . . የቁጥሮች ሁሉ አናሳ ዜሮ በሙሉ ቁጥሮች ስሌት ወቅት ቀዳሚውን የፊት ወንበር ትቆናጠጥ እንጂ፣ ዋጋ ባላቸው የመቁጠሪያ ቁጥር መገልገያዎች እርሷን ከፊትለፊት ቦታ ያስቀደመ ትርጉም አልባ ድምሮችን ከማንኳተቱ በተጓዳኝ አላዋቂነቱን ያሳብቃል፡፡ ታዲያ . . . አንተና መሰሎችህ አጠቃላይ ሰዋዊ ውጤታችሁ ዜሮ ሆኖ ሳለ ከሁሉም ፊት መቆማችሁ፣ ሙሴነትን መተግበራችሁ ይቅርና ለማሰብ መነሳሳታችሁ ራሱ ከስህተት በላይ ነው፡፡ 
ዜሮ ከፍ ካሉ ቁጥሮች መካከል አለያም ከበስተኋላ በተከታይነት ስትቆም የምታሳየውን ትርጉም አዘል ለውጥ አስተውል፡፡ ራስ በመሆን ብቻ ሳይሆን ጭራ በመሆንም ግዙፍ ለውጥ አምጪ ታሪክ መስራት ይቻላል፡፡ ራስህን ሁን፡፡ ››

Thursday, August 14, 2014

አጣብቂኝ



ላለው ይጨመርለታል። ብር ላለው ወርቅ፤ ጠገራ ላለው ማርትሬዛ፤ መከራ ላለው ፍዳ ይጨመርለታል። ትላንት የተጨመሩለትን አሰበ። በዲግሪ ላይ ስራ፤ በስራ ላይ ረብጣ፤ በገንዘብ ላይ ቆንጆ ሚስት፤ በሚስት ላይ ውብ ልጅ ተጨምረውለታል። ደስታቸውን እያጣጣመ አልፏቸዋል። በሚገባ ተጠቅሞባቸዋል። ኖሯቸዋል።

ሁለተኛውን ምዕራፍ ግን በአግባቡ ማስተናገድ አቃተው። ሳቅን የሚያውቅ የልቅሶን ጣዕም ለመረዳት ከሳቁ መንፈስ በሀሳብም በምግባርም መውጣት እንዳለበት ዘነጋ። እሱ መከራ፣ ፈተና . . . ብሎ የገለጸውን የህይወት ክፍል በብቃት መተወን ተሳነው። ቀድሞ በበጎ ገጹ ሳለ“ተጨመረልኝ” ሲል በ ‘ለኔ’ የገለጸውን አሁን“ ተጨመረብኝ” በማለት በ ‘እኔ ላይ’ አደረገው።

በትላንትናው ውስጥ የገነባው የኑሮ ግንብ የእንቧይ ካብ የሚሆንባቸውን ምክንያቶች በቅደም ተከተል ደረደረ።
*ውብ ፍሬው ካለማወቅ ብርሀን ታመልጥ ዘንድ፤ ክፉውን እና በጎውን በሚያስለየው የዕውቀት ጠበል ትጠመቅ ዘንድ እንዳትችል ኪሱ ከስቷል።

Monday, August 4, 2014

አየህ ወዳጄ . . .



እንደ ዕድል ሆኖ ዛሬ ከማይክራፎኑ ጅርባ ነህ፡፡ እንዳጋጣሚ ሆኖ ብዕርህ የብዙዎችን አትኩሮት ስቧል፡፡ወደውም ሳይወዱም ይሰሙሀል፡፡ ምርጫ ያጣም አማራጭ የፈለገም ያነብሀል፡፡

 እዚህ ጋር ቆም ብለህ አስብ . . .

ይህ ውድ መዓድ፣ በርካቶች ፈልገው ያጡት፤ በርካቶች ከኔ የተሻለ ይጠቀምበት ብለውበትህትና ያለፉት መድረክ የተከበረ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ነገር ተበላሽቶ ማንም ፈነጨበት እንጂ . . .

Friday, April 11, 2014

መናጆ


በርካታ በጎች ያሉት ሰው አለ እንበል። ካሉት በጎች መካከል አንዷን ነጥሎ መሸጥ ፈልጓል። ለመሸጥ ያሰባትን በግ ከመንጋዋ ነጥሎ ለመውሰድ ግን አይቻለውም፤የበግ ተፈጥሮ እንዲያ አይደለማ . . .በግ ተከታትሎ ነው መንገድ የሚወጣው - በግ በደቦ ነው የሚጓዘው። በግን በአዲስ ጎዳና ለማራመድ የከጀለ ማንም ሰው የሚጠበቅበት ከመካከላቸው አንዷን ጎተት አድርጎ በታቀደው ቦታ እንድታልፍ ማድረግ በቂ ነው። ከዚያ የተቀሩት ተግተልትለው ያልፋሉ። ተከታትለው ያዘግማሉ። 

ስለዚህ ያ ሰው  - ያ በግ ነጋዴው ግለሰብ - የሚሸጠው አንዷን በግ ብቻ እንደሆነ እያወቀ . . .  ቀሪዎቹን ይዞ እንደሚመለስ እያወቀ . . . ሌሎች ሶስት አራት አጃቢዎችን (መናጆ) ይዞ ገበያ ይወጣል።  የምትሸጠው በግ የታለመላትን ተግባር እስክታከናውን የተቀረው ጀሌ የገባችበት ሲገባ የወረደች የወጣችውን ሲመላለስ ይውላል። ተሻጯ ፈላጊ እስክታገኝ ይከተላል። ይህ ተግባር የሚያቆመው መናጆ አስከታይዋ አላማዋን ከግብ እስክታደርስ ነው። ሌላ ተሻጭ - ሌላ መናጆ አስከታይ እስኪፈጠር የተቀረው በግ ወደ በረቱ ይመለሳል።

Wednesday, April 9, 2014

ለሚመለከተው ሁሉ

አዎ አንተ የተማርክ ነህ!  ከአንድም ሁለት ሶስት ተቋማት ውስጥ ገብተህ አንደኛ ፣ ሁለተኛ ፣ እያልክ ዲግሪዎችን ደርድረሀል። ‘አንቱ’’ ተብለሀል። ሀገርህ ካሏት ’ ምሁራን’ መካከል ቀዳሚዎቹ ረድፍ ላይ አለህበት።

አዎ አንተ አንባቢ ነህ! ከትምህርት ቤት ከወጣህ ማግስት ጀምሮ በአዲስ ሀሳብ ውስጥህን ለመሙላት፤ የያዝከውን ጅምር እውቀት ለማስፋት፤ ልዩ ልዩ አስተሳሰቦችን ለመገንዘብ ቀን ከሌት ትታትራለህ።