Friday, October 11, 2013

ፍተላ

በአንድ ቲያትርን በሚያስተምር መንግስታዊ ተቋም የሚሰለጥን ሰው ነው። ፒሪሪም ፓራራም ለተባለ ፊልም በተዋናይነት ይታጫል። ታጭቶም አልቀረም ስክሪን ቴስት አድርጎ ያልፋል። ይተውናልም . . . 

የተሰጠችው ቦታ አጠር ያለች ብትመስልም ረዘም ላሉ ደቂቃዎች አንድ ለበለጡ ቀናት ይቀረጻል። ፊልሙ የዝግጅት ጣጣውን ጨርሶ ለእይታ ሲበቃ ሰዎችን እንዲጋብዝ የተሰጠው ወረቀት ፊልሙ ላይ ካለው ቦታ የበለጠ ነበር። የቀረው ዘመድ አዝማድ የለም። አብረውት የሚማሩ በሙሉ ታዳሚዎች ናቸው።
 
ለአብዛኞቹ እሱ ለጋበዛቸው እድምተኞች አንድ ቀን ከምናምን ሙሉ ያሳለፈውን አድካሚ የቀረፃ ጊዜ ተርኳል። ስክሪፕቱን ለመያዝ የፈጀበትን ጊዜ አውርቷል። የዳይሬክተሩን ቁጡነት ለፍፏል። ስለተዋንያን፣ ስለካሜራ ደስኩሯል።
አሁን ፊልሙ በመታየት ላይ ነው።  አጋማሹ ላይ የደረሰ ቢሆንም ተዋናዩ እስካሁን አልታየም። ከግማሽ አልፎ ወደመጠናቀቁ ሲቃረብ ተዋናዩ ውልብ ብሎ ጭልም ቢልም፣ ጥቂት ቃላትን ተናግሮ ድምጹን ቢያሰማም ያላስተዋሉት በዙ።   
               
                    ‘’ታይቷል!’’ ‘’አልታየም!’’ እያሉ የሚከራከሩ በረከቱ።

በበነጋው የተቀረጸው ብዙ እንደነበር ነገር ግን ሰዓት ለማሳጠር እና በአናዳንድ የኤዲቲንግ ስህተቶች ምክንያት በዚህ መልኩ እንዳጠረ . . . ይህ በመሆኑም ፕሮሪውሰሩን እና ዳይሬክተሩን ጨምሮ በርካታ የፊልሙ አባላት እንዳዘኑ ለወዳጆቹ ለማስረዳት እያሰበ ወደሚማርበት ቦታ ሲደርስ- ምክንያቱን ከመግለፁ በፊት፣ ችግሩን ከማስረዳቱ በፊት፣ ምንም ከማለቱ ምንም ነገር ከማድረጉ በፊት ጥቁር ሰሌዳው ላይ የተፃፈውን ሲያነብ ቅስሙ የተሰበረው - የተበሳጨውና የተናደደው - ነገርየው የተባለው እሱ ለይ በመሆኑ እንጂ ባይሆን ኖሮ ከተከት ብሎ በሳቀ ነበር። ጥቁሩ ግድግዳ ላይ በነጭ የተነቀሰው ጽሁፍ እንዲህ የሚል ነው።

የአፋልጉኝ ማስታወቂያ

ወዳጃችን እከሌ እከሌ ፒሪሪም ፓራራም የተባለ ፊልም ላይ ገብቶ የገባበት ስለጠፋብን ያለበትን የሚያውቅ ካለ ቢጠቁመን ወሮታውን የምንከፍል መሆኑን እንገልጻለን።


Wednesday, August 28, 2013

በመካነ ፊት (facebook) መንደር በዓጭር ጊዜ ውስጥ ታዋቂ ጦማሪ ለመሆን የሚያስችሉ 5 ነጥቦች


ክቡር ጦማሪ ሆይ፡- መቼም በሆነ የታሪክ አጋጣሚ ዘመኑ በፈቀደልን ስሜትን የመግለጫ፣ ሀሳብን የማስተላለፊያ መንገዶች በመጠቀም የልባችንን መተንፈስ ከጀመርን ሰነባበተ እነሆ እኔም ሳይገባኝ ወደላይ ተንጠራርቼ ምክር ለመለገስ ዳዳኝ። አንተም እንደምታውቀው ባለፈው ጊዜም ፓስት አድርገህ እንዳየሁት <<ሰዎች ለሰዎች ያለስስት የሚለግሱት ነገር ምክር ነው!>> እናም ታናሽነቴን ሳታይ የምለውን እንደምትቀበለኝ ተስፋ አደርጋለሁ።

1ኛ- የህዝቡን የልብ ትርታ አዳምጥ፡-
 
ሰሞነኛ ትኩሳቶችን እየተከታተልክ የሚመስልህን ነገር በፍጥነት እና በተከታታይ በገፅህ ላይ ማስፈር ተገቢ ነው። ነገርየው የምታምንበት ባይሆንም እንኳን አጋጣሚው በርካታ 'ላይኮች'ን ሊያስገኝልህ ስለሚችል ተመሳሳይ ገጠመኞችን በቀላሉ ማለፍ አይገባም። የፖለቲካም ሆነ የሀይማኖት፤ የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ ፤የኪነጥበብም ሆነ የእስፖርት፤ የግለሰብም ሆነ የድርጅት፤ የቡድንም ይሁን የተቋም ሰሞነኛ ወሬዎችን አትለፍ። ፍላጎት የለኝም፣ ስለጉዳዩ የማውቀው ነገር የለም፣ በቂ መረጃ አልሰበሰብኩም ወዘተ … የሚሉ ተልካሻ ምክንያቶችን አስወግድ ብታውቅም ባታውቅም ቢጥምህም ባይጥምህም ብታምንበትም ባታምንበትም ፃፍ።

2ኛ ደፋር ሁን፡- 

Monday, August 26, 2013

አበል ለዘላለም ትኑር!


የሀይስኩል ተማሪ በነበርኩበት ጊዜ ነው። በእድሜ ገፋ ያሉት መምህር እጃቸው በቾክ ተጨማልቆ - ብላክቦርዱን መለየት በማይቻሉ እና በተዘበራረቁ መስመሮች፣ ቅርጾች፣ ቁጥሮች፣ ፊደላት አጨማልቀው እያስተማሩ ነው። እያስረዱ ነው። የተማሪው ፊት ላይ የተመከቱት ሁኔታ ግን እንዲቀጥሉ የሚገፋፋ አልነበረም። ተማሪው ፊት ላይ ድብርት ይነበባል። መምህሩ በድንገት ማስረዳታቸውን አቁመው ያልተለመደ ጥያቄ ጠየቁ

“ይህንን ትምህርት መማራችሁ ለምን ይጠቅማችኋል?” ጉዳዩ በክፍሉ መነቃቃትን ፈጠረ። “ግን ይሄ ሳብጀክት ለምን ይጠቅማል?”

መምህሩ እጅ ያወጣን ተማሪ ብቻ ሳይሆን አርፎ የተቀመጠንም ማፋጠጥ ይዘዋል።
“ይህንን ሳብጀክት ለምን ትወስዳላችሁ? ህይወታችሁ ላይ ምን ይጨምራል?”
ነገርየው አሳፋሪ ቢሆንም ከ50 የሚበልጠው እና ደብተሩ ላይ እየጻፈ፣ መፅሀፍ እያነበበ፣ ሰዓት ጠብቆ እየገባ፣ እያጠናና እየተፈተነ የሚወስደውን ኮርስ ምን እንደሚጠቅመው አያውቅም።
መምህሩ ንዴት፣ ብስጭት፣ መገረም እጠየተነበበባቸው ይዘውት የመጡትን ጓዝ ሸክፈው ወደመውጫው በር አመሩ።