Friday, August 22, 2014

0(ዜሮ)


‹‹ከቁጥሮች መካከል የመጨረሻውን ባዶ ደረጃ የያዘችው ‘0’ ናት፡፡ አንተም በሰው ልጆች የዕውቀት፣ የዐስተሳሰብና የዐመለካከት መስፈርቆች ስትገመገም ማርክህ ዜሮ ቢሆን ’ዋጋ የለኝም’ አትበል፡፡
ያቺ . . . የቁጥሮች ሁሉ አናሳ ዜሮ በሙሉ ቁጥሮች ስሌት ወቅት ቀዳሚውን የፊት ወንበር ትቆናጠጥ እንጂ፣ ዋጋ ባላቸው የመቁጠሪያ ቁጥር መገልገያዎች እርሷን ከፊትለፊት ቦታ ያስቀደመ ትርጉም አልባ ድምሮችን ከማንኳተቱ በተጓዳኝ አላዋቂነቱን ያሳብቃል፡፡ ታዲያ . . . አንተና መሰሎችህ አጠቃላይ ሰዋዊ ውጤታችሁ ዜሮ ሆኖ ሳለ ከሁሉም ፊት መቆማችሁ፣ ሙሴነትን መተግበራችሁ ይቅርና ለማሰብ መነሳሳታችሁ ራሱ ከስህተት በላይ ነው፡፡ 
ዜሮ ከፍ ካሉ ቁጥሮች መካከል አለያም ከበስተኋላ በተከታይነት ስትቆም የምታሳየውን ትርጉም አዘል ለውጥ አስተውል፡፡ ራስ በመሆን ብቻ ሳይሆን ጭራ በመሆንም ግዙፍ ለውጥ አምጪ ታሪክ መስራት ይቻላል፡፡ ራስህን ሁን፡፡ ››

Thursday, August 14, 2014

አጣብቂኝ



ላለው ይጨመርለታል። ብር ላለው ወርቅ፤ ጠገራ ላለው ማርትሬዛ፤ መከራ ላለው ፍዳ ይጨመርለታል። ትላንት የተጨመሩለትን አሰበ። በዲግሪ ላይ ስራ፤ በስራ ላይ ረብጣ፤ በገንዘብ ላይ ቆንጆ ሚስት፤ በሚስት ላይ ውብ ልጅ ተጨምረውለታል። ደስታቸውን እያጣጣመ አልፏቸዋል። በሚገባ ተጠቅሞባቸዋል። ኖሯቸዋል።

ሁለተኛውን ምዕራፍ ግን በአግባቡ ማስተናገድ አቃተው። ሳቅን የሚያውቅ የልቅሶን ጣዕም ለመረዳት ከሳቁ መንፈስ በሀሳብም በምግባርም መውጣት እንዳለበት ዘነጋ። እሱ መከራ፣ ፈተና . . . ብሎ የገለጸውን የህይወት ክፍል በብቃት መተወን ተሳነው። ቀድሞ በበጎ ገጹ ሳለ“ተጨመረልኝ” ሲል በ ‘ለኔ’ የገለጸውን አሁን“ ተጨመረብኝ” በማለት በ ‘እኔ ላይ’ አደረገው።

በትላንትናው ውስጥ የገነባው የኑሮ ግንብ የእንቧይ ካብ የሚሆንባቸውን ምክንያቶች በቅደም ተከተል ደረደረ።
*ውብ ፍሬው ካለማወቅ ብርሀን ታመልጥ ዘንድ፤ ክፉውን እና በጎውን በሚያስለየው የዕውቀት ጠበል ትጠመቅ ዘንድ እንዳትችል ኪሱ ከስቷል።

Monday, August 4, 2014

አየህ ወዳጄ . . .



እንደ ዕድል ሆኖ ዛሬ ከማይክራፎኑ ጅርባ ነህ፡፡ እንዳጋጣሚ ሆኖ ብዕርህ የብዙዎችን አትኩሮት ስቧል፡፡ወደውም ሳይወዱም ይሰሙሀል፡፡ ምርጫ ያጣም አማራጭ የፈለገም ያነብሀል፡፡

 እዚህ ጋር ቆም ብለህ አስብ . . .

ይህ ውድ መዓድ፣ በርካቶች ፈልገው ያጡት፤ በርካቶች ከኔ የተሻለ ይጠቀምበት ብለውበትህትና ያለፉት መድረክ የተከበረ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ነገር ተበላሽቶ ማንም ፈነጨበት እንጂ . . .