ቀደም ባለው ጊዜ በሐገራችን የሚሰራጩ የሬዲዮ እና የቴሌቪዥን ጣቢያዎቻችን ቁጥር አነስተኛ ነበር፡፡ ከ 16ዓመት በፊት FM 97.1 ሳይጀመር፤ ጣቢያዎቹ የሚያስተላልፏቸው ፕሮግራሞች በህብረተሰቡ ዘንድ ያላቸው ተቀባይነት ደግሞ ከፍተኛ ነበር፡፡ የዕጅ ሰዓትን ለመሙላት ሳይቀር ማንጸሪያ እና መከራከሪያ ነጥቡ ከራዲዩ እኩል መሆኑ ነበር፡፡ አሁን በርከት ያሉ የራዲዮ ጣቢያዎች ባለቤት ነን፡፡ /የግልም የመንግስትም/ ለኢትዩጵያዊ ታዳሚ እንዲደርሱ ታልመው የሚሰናዱ የሳተላይትና የሀገር ውስጥ ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ቁጥርም በማሻቀብ ላይ ነው፡፡ የተአማኒነቱ ጉዳይ ግን ቀስ በቀስ እየተሸረሸረ መጥቷል፡፡ ዛሬ ዛሬ በራዲዮ ድምጽን ማሰማት የጥቂት ደቂቃዎች ሙከራ ውጤት ነው፡፡ እንደቀደመው ዘመን ከፍ ያለ ትጋት አይጠይቅም፡፡