ዘመናችንን በጥበብ ለመቃኘት የጀመርነውን ጉዞ ስንቀጥል የዛሬ ማረፊያችንን ተወራራሽ ጥበባት ላይ አድርገናል፡፡ በኪነ-ጥበቡ ዓለም አንድን ጥበባዊ ሥራ መነሻ በማድረግ፤ ወይም ሃሳቡን በሌላ ያልታየበት አቅጣጫ በማየት፤ ወይም ሙሉ ስራውን ወስዶ በሌላ የጥበብ ዘውግ መግለጽ እንግዳ ተግባር አይደለም፡፡
‹‹የማዕበል ዋናተኞች›› የተሰኘው የራዲዮ ድራማ ተዘፍኖለታል፡፡ ድርሰቱ የሐይሉ ጸጋዬ ነው፡፡ በወቅቱ ከፍተኛ ተደማጭነት የነበረው ሲሆን በበርካታ ታዳሚያን ልብ ውስጥ ለመግባት የቻለ ነበር፡፡ ድራማው ሲጠናቀቅ የዋናዋን ገጸባህሪ ስም ‹‹ዕፁብ ድንቅ›› ስያሜው በማድረግ ግሩም ዘፈን ተሰርቷል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ያቀነቀነው ጎሳዬ ተስፋዬ ነው፡፡ ቆይቶ በላፎንቴኖችም ተዘፍኗል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ በቴሌቪዥን ተከታታይ ድራማነት መጥቷል፡፡ ተቀባይነቱ በራዲዮ የነበረውን ያህል መሆኑን ግን እጠራጠራለሁ፡፡